#ከተረጅነት_ወደ_ምርታማነት!...

ዝርዝር ዜና

ጤና ፅ/ቤት
no photo

#ከተረጅነት_ወደ_ምርታማነት!

ሰኔ 10-2017

በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ አስተዳደር "ከተረጅነት ወደ ምርታማነት!" መሪ ሀሳብ የአቃቂ ቂሊንጦ ዶሮ እሴት ሰንሰለት እና የገላን የዶሮ ክላስተር የስራ ማስጀመርያ መርሃ-ግብር ተካሄደ። ሰኔ 10/2017 ዓ.ም (አቃቂ ቃሊቲ) በአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ ወረዳ 4 አስተዳደር በሚገኘዉ የአቃቂ ገላን ዶሮ ክላስተር የምግብ ዋስትና ተጠቃሚ 70 እናቶችን በ7 ማህበር በማደራጀት ይፋዊ የማስጀመርያ መርሃ-ግብር ተካሂዷል። በመርሃ-ግብሩ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ብልጽግና ፓርቲ ጽ/ቤት ኃላፊ ክቡር አቶ ሞገስ ባልቻ፣ በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የስራና ክህሎት ቢሮ ኃላፊ ክቡር አቶ ጥራቱ በየነ፣ የአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ አስተዳደር ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ አለማየሁ ሚጀና፣ የከተማ አስተዳደሩ አርሶ አደርና ከተማ ክብርና ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አቶ መለሰ አሼቦ፣ የክፍለ ከተማው ብልጽግና ፓርቲ ቅ/ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ዮሐንስ ለገሰ፣ የክፍለ ከተማው ምክትል ዋና ስራ አስፈጻሚና የስራ እና ክህሎት ጽ/ቤት ኃላፊ ወ/ሮ ውቢት ዮሐንስ፣ የአዲስ አበባ ከተማ እስተዳደር ካቢኔ አባላት፣ የአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ እና የወረዳ አመራሮች፣ የኃይማኖት አባቶች እና የሴፍቲኔት ተጠቃሚዎች ተገኝተዋል። የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ብልጽግና ፓርቲ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ኃላፊ ክቡር አቶ ሞገስ ባልቻ ባደረጉት ንግግር እንደገለጹት ህልማችን ሁለንተናዊ ብልጽግና ማረጋገጥ ሲሆን ከድህነት እና ከተረጅነት ለመላቀቅ በሰራናቸዉ ዘርፈ ብዙ ተግባራት ባለፉት የለውጥ ዓመታት ውጤት ማስመዝገብ ችለናል ብለዋል። አክለዉም በቀጣይ 90 ቀናት የንቅናቄ ስራዎች አንዱ ተረጅነት እና ልመናን የማስቀረት ተግባር ሲሆን የስራ ባህላችንን በመቀየር እንዲሁም ስንፍናን በማስቀረት ተግተን በመስራት ድህነትን ታሪክ አድርገን የተከበርን ህዝቦች መሆናችንን ለአለም ልናረጋግጥ ይገባል ብለዋል። የአቃቂ ቃሊቲ ክፍለ ከተማ አስተዳደር ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ አለማየሁ ሚጀና የክብር እንግዶች የእንኳን ደህና መጣችሁ የመክፈቻ ንግግር ሲያደርጉ እንደገለጹት በአስተዳደሩ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ውስጥ ለሚገኙ ነዋሪዎች ልዩ ትኩረት ተሰጥቶ ዘርፈ ብዙ ሰው ተኮር ስራዎች በማከናወን ተጠቃሚነታቸውን በማረጋገጥ ላይ እንገኛለን ብለዋል። ዋና ስራ አስፈጻሚው አያይዘውም በዛሬው ዕለት በቂሊንጦ የዶሮ እሴት ሰንሰለት እና የገላን የዶሮ ክላስተር ተጠቃሚዎችን ይፋዊ የማስጀመር መርሃ ግብር የዚሁ ተግባራችን አንዱ ማሳያ ነዉ በማለት በገላን የዶሮ ክላስተር በ7 ሼዶች 10 ሺ 500 ዶሮዎች እንደሚገኙና ተጠቃሚዎች ከራሳቸው አልፈው በቂ ምርት በማምረት ለገበያ በማቅረብ የገበያ ማረጋጋት ስራ እንደሚጠበቅባቸዉ ጠቅሰው በክላስተር ስራው የተሳተፉ ተቋማትን በአስተዳደሩ ስም አመስግነዋል። የክብር እንግዶቹ ቂሊንጦ የዶሮ እሴት ሰንሰልትን የጎበኙ ሲሆን በማዕከሉ ከአንድ ቀን ጫጩት ጀምሮ፣ አሳድጎ ለእርድ ሲደርሱ የዶሮ ስጋን በልቶ ለገበያ ማቅረብ የሚያስችል ማቀነባበሪያ ሲሆን በማዕከሉ በ3 ሼዶች 4 ማህበራት እና 1200 ዶሮዎች ማስፈልፈል የሚያስችሉ ኢንኩቤተሮች የተገጠሙለት መሆኑ ተገልጿል። በክፍለ ከተማው የመስኖ ክላስተር፣ የማር ክላስተር፣ የዶሮ እሴት እና የዶሮ እንቁላል ክላስተር ተሰርቶ ተግባራዊ እየተደረገ መሆኑን እንግዶቹ በማር ክላስተር የመስክ ጉብኝት ባደረጉበት ወቅት ተገልፆላቸዋል።